የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ እና የአዲስ ማዲያ ኔትወርክ አመራሮች በቴሌቪዥን እየተሰጠ የሚገኘው የሒሳብና እንግሊዘኛ የማጠናከሪያ ትምህርት አፈጻጸምን ገምግመዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዘላለም ሙላቱ በአዲስ ማዲያ ኔትወርክ AMN+ በመተላለፍ ላይ የሚገኘው የቴሌቪዥን ትምህርት በከተማ አስተዳደሩ የሒሳብና እንግሊዘኛ ትምህርትን ውጤታማ ለማድረግ የተዘጋጀውን ስትራቴጂ መሰረት አድርጎ ለተማሪዎች በመተላለፍ ላይ መሆኑን ጠቁመው የቴሌቪዥን ትምህርቱ ከተጀመረ በኋላ በተማሪዎች ውጤት ላይ ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን ቢሮው ማረጋገጡን አስታውቀዋል።
ኃላፊው አያይዘውም የቴሌቪዥን ትምህርቱ በሚፈለገው ደረጃ ለተማሪዎች ተደራሽ እንዲሆን የተለያዩ የንቅናቄ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን አስታውሰው ተማሪዎች የማጠናከሪያ ትምህርቱን በአግባቡ ተከታትለው ውጤታማ እንዲሆኑ እስካሁን የነበሩ ጠንካራ ጎኖችን በማስቀጠልና በሂደት የተስተዋሉ ክፍተቶችን በማረም የተሻለ ስራ መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በመርሀግብሩ የስርአተ ትምህርት ማበልጸግና ትግበራ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ታለማ የቴሌቪዥን ትምህርቱን አፈጻጸም ሪፖርት አቅርበው ውይይት ተካሂዷል።
.