የቢሮው የፈተና ዝግጅትና አስተዳደር እና የስርአተ ትምህርት ማበልጸጊያና ትግበራ ዳይሬክተሮች በተገኙበት ውይይት የኢንፎርሜሽን ኮሚኒኬሽን ቴክኖሎጂ ልማት ማስፋፋት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ደረጀ ዳኜ የማስፈጸሚያ እቅዱን አቅርበው ውይይት ተካሂዷል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ክቡር ዶክተር ዘላለም ሙላቱ የ2018 ዓ.ም የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ብሔራዊ ፈተና በከተማ አስተዳደሩ ሙሉ በሙሉ በበይነ መረብ እንደመሰጠቱ ፈተናው ስኬታማ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሁሉም ባለድርሻ አካል ኃላፊነቱን በአግባቡ እንዲወጣ በእቅዱ ዙሪያ በቂ ግንዛቤ መፍጠር እንደሚገባ ጠቁመው ቢሮው በቀጣይ በሁሉም የፈተና ጣቢያዎች የአይ ሲቲ መሰረተ ልማቶችን ዝግጁ ከማድረግ ጀምሮ በቂ የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲኖር ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት የሚሰራ መሆኑን አመላክተዋል።
ኃላፊው አያይዘውም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2017 ዓ.ም የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ብሔራዊ ፈተና ሁሉም ባለድርሻ አካል ኃላፊነቱን በአግባቡ በመወጣቱ ያለምንም እንከን መጠናቀቁን አስታውሰው ዘንድሮ በበይነ መረብ የሚሰጠው ፈተና ስኬታማ እንዲሆን ፈተናውን የሚሰጡ የመንግስም ሆኑ የግል 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት ማድረግ እንደሚገባቸው በመጠቆም በየደረጃው የሚገኙ የትምህርት እና የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት መዋቅሮች ተገቢውን ድጋፍና ክትትል የማድረግ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊና የዘርፉ አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ አበራ በበኩላቸው የማስፈጸሚያ እቅዱ በዋናነት ባለድርሻ አካላትን በማቀናጀትና ተግባርና ኃላፊነታቸውን በማሳወቅ ለፈተናው ማስፈጸሚያ የሚያስፈልጉ ግብአቶችን ከወዲሁ ዝግጁ ለማድረግ እንዲቻል ታስቦ መዘጋጀቱን ገልጸው ቢሮው በቀጣይ በማስፈጸሚያ እቅዱ ዙሪያ በየደረጃው ከሚገኙ ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት የሚያካሂድ መሆኑን አስታውቀዋል።